Sep 24, 2013

በኮንዶሚኒየም ቤቶች ሺያጭ ሥም ስደተኛውን የወያኔ ጭሰኛ ለማድረግ የተጀመረው እንቅስቃሴ ይከሽፋል::

ወያኔ እንደ ድርጅት የሚፈልገውን የፖለቲካ ጥቅም የሚያስገኝለት እስከመሰለው ድረስ በህዝብና በአገር ላይ የማይፈጽማቸው ምንም አይነት እኩይ ተግባሮች እንደማይኖሩ በተግባር ያስመሰከረ ድርጅት ነው::
ለአብነት ያህል ለመጥቀስ ፤
  1. ድርጅቱ ገና ትግራይ በረሃ ውስጥ ትግል ላይ በነበረበት ወቅት የትግራይን ወጣቶች ከትምህርት ገበታቸው እያነቀ በመውሰድ አላማውን በግልጽ ላልተረዱትና ላላመኑበት ጦርነት ማግዶአቸዋል:: በዚህም የተነሳ ወያኔ እራሱ ይፋ ባደረገው አሃዝ ብቻ ቁጥራቸው 60 ሺህ የሆኑ ለጋ ወጣቶች ላለፉት 22 አመታት የህዝባችንን ስቃይና መከራ እያራዘመ ያለውን የድርጅቱን መሪዎች ሥልጣን ላይ አውጥቶ ለማንገስ ከፍተኛ የህይወት መስዋዕትነት ከፍለዋል ::
  2. የአገራችንን ክብርና መልካም ገጽታ እስከዛሬ አበላሽቶ ባለፈው በዚያ አስከፊ የ1977ቱ ድርቅ ወቅት ለትግራይ ተጎጂዎች ከአለም አቀፍ ለጋሾች የተበረከተውን የነፍስ አድን እህል በሱዳን በኩል ወደውጭ አሳልፎ በመቸብቸብ መሪዎቹና ተከታዮቻቸው ለተንደላቀቀ ኑሮ ሲበቁ በብዙ ሺህ የሚቆጠሩ ህጻናት፤ አሮጊቶችና አዛውንቶች እንደቅጠል እንዲረግፉ ምክንያት ሆኖአል::
  3. የትግራይ ህዝብ ተማሮ በመንግሥት ላይ እንዲያምጽ ለመቀስቀስ በደሃው አቅማችን የተገነቡ ትምህርት ቤቶችን፤ የህክምን አገልግሎት መስጫ ተቋሞችን ፤ ድልድዮችንና ሌሎች መሠረተ ልማቶችን በፈንጂና በመድፍ ከማውደም አልፎ የተሳሳተ መረጃ ለደርግ በመስጠት ቁጥራቸው በውል ያልታወቀ ህዝብ ለገበያ እንደወጣ ሃውዜን ከተማ ላይ በጠራራ ጸሃይ እንዲጨፈጨፍ አድርጎአል::
  4. የደርግ አገዛዝ ከተወገደ ቦኋላ ሥልጣን ላይ ለመደላደል የሚያስችል ድጋፍ ለመሸመት ሲባል የአገራችንን ሉአላዊ ጥቅም ለባዕድ አሳልፎ የሰጠ በርካታ ግልጽና ድብቅ ውሎችን ከ3ኛ አካላት ጋር ፈጽሞአል :: ከውሎቹ አንዱ የህዝባችንን ትኩረት ለማስለወጥ ካለፈው 2 አመት ጀምሮ በሰፊው እየተዘመረለት የሚገኘው የአባይ ወንዝን የመጠቀም መብታችንን የሚጻረር እንደነበረ ጉልህ ማስረጃ አለ::
  5. በሚሊዮን የሚጠጋ ህዝባችንን ከቀያቸው በማፈናቀል ለም መሬታችንንና ድንግል የተፈጥሮ ሃብታችንን ለህንድ ፡ ለቻይናና ለአረብ ከበርቴዎች በመቸብቸብ በገዛ አገራችን የባዕድ አሽከር እንዲንሆን ፈርዶብናል::
  6. በመቶ ሺዎች የሚቆጠሩ ሴት እህቶቻችን ለባርነት ሥራ ወደ አረብ አገር በመላክ ከፍተኛ ሰቆቃ እንድፈጸምባቸው በማድረግ ብሄራዊ ክብራችንን ኩራታችንን የሚያጎድፍ ተግባር ፈጽሞአል::
  7. በሙስናና ዘረፋ የተጨማለቀ ሥርዓት በማቋቋም አብዛኛው ህዝባችን ከወለል በታች ወደወረደ የድህነት አረንቋ ውስጥ ገብቶ የቁም ስቃይ እንዲቀበል አድርጎአል::
  8. መብታቸውን ለማስከበር በጠየቁ ወገኖቻችን ላይ እስከ አፍንጫው የታጠቀ ጦር በማዝመት በርካቶችን አስጨፍጭፎአል፤ ከቤት ንብረታቸው አፈናቅሎአል ፤ ለእስርና ለስደት ዳርጎአቸዋል:: ወዘተ
ወያኔ ይህንንና ግዝፈታቸው ከዚህ የከበዱ በርካታ ሰቆቃዎችን በአገርና በወገን ላይ እየፈጸመ የአገዛዝ ዘመኑን ሊያራዝም የቻለው፤
  1. ህዝባችን በዘር ፤ በቋንቋና በሃይማኖት ተከፋፍሎ እርስ በርሱ እንዳይተማመንና የጎሪጥ እንድተያይ ሌት ተቀን ተንኮል በመሸረቡ
  2. የጦር ሃይል ፤ የፖሊስ ሠራዊት፤ የደህንነትና ሌሎች የኢኮኖሚና ማህበራዊ አገልግሎት መስጫ ተቋሞች በሙሉ ከአንድ አካባቢ በተሰባሰቡ የጥቅም ተጋሪዎች ቁጥጥር ሥር እንዲወድቅ ተደርጎ እሺ ያለውን በጥቅም እምቢ ያለውን ደግሞ በጠመንጃ ሃይል ጸጥ ለጥ ለማድረግ በመመኮሩ፤
  3. ከራሳቸው የግል ሚቾትና ቅንጦት አሻግረው በወገንና በአገር ላይ እየተፈጸመ ያለውን ሰቆቃ ማየት የማይፈልጉ ወይም የማይችሉ ተፈጥሮአዊ ባህሪያቸው “ እኔ ከሞትኩ ሠርዶ አይብቀል “ ካለቺው እንስሳ የማይለይ ሆዳሞች ከተለያየ የህበረሰተሰብ ክፍል ተመልምለው ከአገዛዙ ዙሪያ በሎሌነት ለመሰለፍ በመቻላቸው እንደሆነ ይታወቃል::
በሌላ አገላለጽ ወያኔ የአገዛዝ እድሜውን ለማራዘም የፈጸመውና እየፈጸመ ያለው ቀደም ሲል ፋሽስት ጣሊያን የአገራችንን ህዝብ በባርነት ለመግዛት አድርጋው ከነበረው ቅስም ሰባሪ እርምጃዎች በባህሪም ሆነ በአይነት አንድ መሆኑ ግልጽ ነው:: ለመብቱና ለነጻነቱ ቀናዕ የሆነው የኢትዮጵያ ህዝብ ግን ትናንት ለጣሊያን መደለያዎች ተታሎ ወይም የሃይል እርምጃ ተንበርክኮ ነጻነቱን አስነጥቆ ለመኖር እንዳልፈቀደ ሁሉ ዛሬም ከአገሩ የሰሜን ክፍል የበቀሉ ባንዳዎች በጉልበታቸውም ሆነ ሌሎች መሸንገያዎች የሚያደርጉትን አሜን ብሎ እስከወዲያኛው ለመገዛት ፈቃደኛ አለመሆኑን በሚያደርገው ተቃውሞ እየገለጸ ነው::
ይህንን ሃቅ የተረዳው ወያኔ የጭቆና ክንዱን ለማፈርጠም የሚያስፈልገውን ገንዘብ በስደት ውጭ አገር ከሚኖረው ኢትዮጵያዊ ለመሰብሰብና የተቃውሞ እንቅስቃሴውን ለማዳከም በኮንዶሚኒየም ቤት ሽያጭ ሥም አዲስ እቅድና ስልት ነድፍ መንቀሳቀስ ጀምሮአል::
ብቸኛው የፓርላማ ተወካይ የሆኑት አቶ ግርማ ሠፉ በቅርቡ ከኢሳት ሬዲዮ ጋር ባደረጉት ቃለመጠይቅ እንዳረጋገጡት ወያኔ በስደት ለሚኖረው ኢትዮጵያዊ የነደፈው የኮንዶሚኒየም ቤት ሺያጭ ዋና አላማ አገር ቤት ውስጥ እየተፏፏመ የመጣውን ህዝባዊ ተቃውሞ ለመምታት በተለያዩ የምዕራብ አገሮች ከፍ ብለው እየተደመጡ ያሉትን ድምጾች አሰቀድሞ ለማዳከም በመፈለጉ እንደሆነ አያጠራጥርም::
ምንም እንኳን ለራሳቸው ማንነትና ስብእና ክብር የሌላቸው አንዳንድ ዜጎች “የአባትህ ቤት ሲዘረፍ አብረህ ዝረፍ” በሚል ፈሊጥ በዚህ የወያኔ ወጥመድ ውስጥ ለመውደቅ ውር ውር እያሉና በየአገሩ የሚገኘውን የወያኔ ኤምባሲ በር ማንኳኳት የጀመሩ መኖራቸው ባይካድም አንድ ወቅት ላይ ግር ግር ፈጥሮ ወዲያው እንደተጨናገፈው የአባይ ቦንድ ሺያጭ የታሰበውን ያህል ውጠት እንደማያስገኝ በእርግጠኝነት መናገር ይቻላል::
ግንቦት 7 የፍትህ የነጻነትና የዲሞክራሲ ንቅናቄ በስደት የሚኖረው ሁሉም ኢትዮጵያዊ አገሩንና ወገኖቹን ጠልቶ ሳይሆን የተሰደደው ለዘመናት የዘለቀው ኢፍትሃዊነት የፈጠረው ኋላ ቀርነትና ድህነት አገሩ ላይ ለመኖር ያለውን ምኞትና ተስፋ አጨልሞበት አለያም በፖለቲካ ችግር ምክንያት ህይወቱን ለማቆየት ተገዶ ነው ብሎ ያምናል::
በዚህም የተነሳ ማንኛውም ስደተኛ ስደት የሚያስከትለውን ማህበራዊና ሥነ ልቦናዊ ቀውሶች ተቋቁሞ አንድ ቀን አገሬ ገብቼ ከወገኖቼ ጋር በሠላም እኖርበታለሁ ብሎ ያጠራቀማትን ጥሪት በከፍተኛ ንቅዘትና ሙሰኝነት ወደ መጨረሻው ታሪካዊ ሞቱ እየወረደ ያለውን የወያኔ ሥርዓት ተማምኖ በማውጣት ቦኋላ እንዳይጸጸት ወገናዊ ምክሩን ይለግሳል::
ወያኔ ለዲያስፖራው ያዘጋጀው የኮንዶሚኒዬም ቤቶች ሺያጭ የፖለቲካ ድጋፍ ለማግኘት የታለም የከተማና የገጠር ህዝባችንን የወያኔ ጭሰኛ ያደረገ የአገር ውስጥ ፖሊሲ አካል ነው:: ከ7 አመት በፊት ኮንዶሚኒዬም ቤት ለማግኘት ለተመዘገቡ 800 ሺህ የአዲስ አበባ ከተማ ነዋሪዎች ያልተዳረሰ ቤት እንዴትና በምን ስሌት ነው በሰው አገር ያውም በአንጻራዊ ምቾት ለምንኖር ዜጎች የታሰበልን ብሎ እራስን መጠየቅ ከትዝብትና ከታሪክ ተወቃሽነት የሚያድን ተግባር ነው ::
ሃብት በተትረፈረፈበትና የሚበላ የሚጠጣ ነገር ከሰው ተርፎ ቆሻሻ ገንዳ ውስጥ በሚጣልበት አሜሪካና አውሮጳ ለምንኖር ዜጎች ከሚስኪኑ ህዝባችን ጉሮሮ በተነጥቀ ገንዘብ ቤተመንሥት ውስጥ ተዘጋጅቶ የተላከ ምግብና መጠጥ ለመደለያነት ሲያጓጉዝ የኖረ መንግሥት አሁን ደግሞ በኮንዶሚኒየም ቤት ሥም ቢመጣብን ጥፋቱ የሱ ሳይሆን የእኛ ለክብራችንና ለነጻነታችን ዋጋ የማንሰጥ ስግብግቦች መሆኑን ምን ጊዜም መዘንጋት የለበትም::
ግንቦት 7 የፍትህ የነጻነትና የዲሞክራሲ ንቅናቄ በስደት ውጭ አገር የሚኖር ማንኛውም አገር ወዳድ ኢትዮጵያዊ ወያኔ በኮንዶሚኒዬም ቤት ሽያጭ ሥም ትግሉን ለማዳከም የዘረጋውን ይህንን የተንኮል ሴራ እንዲያከሽፍ ወገናዊ ሃላፊነት እንዳለበት ያስገነዝባል::
ድል ለኢትዮጵያ ህዝብ !

No comments:

Post a Comment