Mar 1, 2013

ጉዳዩ ቤተ ክርስቲያን ነጻ ናት ነጻ አይደለችም የሚለው ነው


ደጀ ሰላም ከወራት በፊት አቡነ ማትያስ እንደሚሾሙ ያሳወቀችው እውን ሆኗል፤


አዎን፤ አቡነ ማትያስ 6ኛ ፓትርያርክ ሆነዋል

  •      ደጀ ሰላም እያካሄደች ባለችው መደበኛ ያልሆነ “የድረገጽ” ድምጽ አሰጣጥ አቡነ ማቴዎስ ብዙ መራጭ አግኝተዋል፤
  •     ምርጫውን ለሚቃወሙትም፣ ለሚደግፉትም ቀጣዩ ጉዞ እንዴት ይሆናል? እንዴትስ መሆን አለበት?
  •      በውጪ አገራት ካሉ ምእመናን፣ ካህናትና አብያተ ክርስቲያናት የሰከነና የጋራ የሆነ ዘላቂ መፍትሔ ይጠበቃል፤
  •      ውጪ አገር ካለው ሲኖዶስ የበሰለና ለቤተ ክርስቲያን አንድነትና ህልውና የሚበጅ አቅጣጫ ይጠበቃል፤
  •      ድራማው ተጠናቋል፣ ውይይቱ ይቀጥላል።
    (ደጀ ሰላም፤ የካቲት 21/2005 ዓ.ም፤ ፌብሩዋሪ 28/2013/PDF)፦ አምስቱን እጩ ፓትርያርኮች ያካተተው የ6ኛው ፓትርያርክ ምርጫ የአኃት አብያተ ክርስቲያናት ተወካዮችን ጨምሮ ከቅዱስ ሲኖዶስ አባላት ጀምሮ በየደረጃው ድምጽ መስጠታቸው ከተረጋገጠ በኋላ እንደተጠበቀው ብፁዕ አቡነ ማትያስ ዘኢየሩሳሌም እንዳሸነፉ ይፋ ሆኗል።


    ከወራት አስቀድሞ ደጀ ሰላም የውስጥ ምንጮችን ጠቅሳ ባቀረበችው ዘገባ ብፁዕነታቸው የሚቀጥለው ፓትርያርክ እንዲሆኑ በመንግሥት መታጨታቸውን ዘግባ ነበር። በወቅቱ እርሳቸውን ለፓትርያርክነት የሚያሰብ ብዙም ወገን ስላልነበረ የደጀ ሰላም ዘገባ ከተሳሳተ ምንጭ የተገኘ እንደሆነ ብዙዎች ሊያስረዱን ሞክረው ነበር። አሁን ግን “ያልተከደነው ተገለጠ፣ የሚታየው ደግሞ ታየ”።

    ለረዥም ጊዜ እንደታየው፣ ብዙዎች ቀጣዩ ፓትርያርክ አቡነ ሳሙኤል ይሆናሉ ወይም አቡነ ጎርጎርዮስ የሚል የተሳሳተ ግምት ነበረው። ሁለቱም የጨዋታው አዳማቂዎች እንጂ በጨዋታው ውስጥ ቦታ አልነበራቸውም። ወይም ርዕስ መሆናቸው በራሱ የጨዋታው አንድ አካል ነበር። ብዙ ሰው አሁንም ከጠቅላላው ድራማ አንዱ ክፍል ላይ ብቻ በመከራከር ጊዜውን እያጠፋ ነው። ለአንዳንዶች አቡነ ሳሙኤል ወይም የሚፈልጉት አንድ ሌላ አባት ቢሆን ምርጫውን በደስታ የሚቀበለው ይሆንና አቡነ ማትያስን ሊኮንን ይጀምራል። ጉዳዩ እርሱ አይደለም። ጉዳዩ ቤተ ክርስቲያን ነጻ ናት ነጻ አይደለችም የሚለው ነው። ሌላው ያንን ተከትሎ ይመጣል።

    ይህ በእንዲህ እንዳለ ደጀ ሰላም ባካሔደችው “ኢ-ቀጥተኛ” የምርጫ ድምጽ አሰጣጥ ከመረጡት መካከል ብፁዕ አቡነ ማቴዎስ በከፍተኛ ድምጽ ተመርጠዋል። ብፁዕ አቡነ ዮሴፍ የሁለተኛነት ሥፍራ አግኝተዋል። ይህ ምን ያሳይ ይሆን? እንመለስበታለን። አስተያየታችሁን፣ ጥያቄያችሁንና ምልከታችሁን ላኩልን። ድራማው ተጠናቋል፣ ውይይቱ ይቀጥላል።



    ቸር ወሬ ያሰማን አሜን

    No comments:

    Post a Comment