Mar 21, 2013

በደም እንደመጣን በደም ነዉ የምንወጣዉ!!! ህዉሃት





የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ የመራጮችን ምዝገባ አካሂዶና ለተፎካካሪዎችም ምልክት ሰጥቶ ዝግጅቱን አጠናቋል፡፡ በቅርቡም ተፎካካሪዎች ፖሊሲያቸውንና ፖለቲካዊ ርዕዮተ ዓለማቸውን ለሕዝብ የሚያስተዋውቁበት የሰዓት ድልድል አድርጎ የምርጫ ቅስቀሳ ተጀምሯል፡፡

ስሜት እና ቁጥር ለየቅል?
ወ/ሮ ዘርዬ በለጠ ዕድሜያቸው 39 ሲሆን የቤት እመቤት ናቸው፡፡ በኮልፌ ቀራንዮ ክፍለ ከተማ ይኖራሉ፡፡ ሕዝቡም ሆነ መንግሥት ለምርጫው የሰጡት ትኩረት ይህን ያህል አይደለም ይላሉ፡፡ ‹‹ይህ ምርጫ ምንም ይሁን ምን በብዙኅኑ ዘንድ በውል የታወቀ አይመስለኝም፡፡ ለማንኛውም ምረጡ ተብለን እስከተጠየቅን ድረስ መምረጥ ተገቢ ነው ብዬ ስለማስብ እመርጣለሁ፡፡ ማንን ልምረጥ? ማን ምን ይሁን? ማን ከማን ጋር ይፎካከር? ግን ምንም መረጃ የለኝም፡፡ እኔም ፈልጌ አላጣራሁም፤›› ይላሉ፡፡

ከአንድ ምርጫ ዲሞክራሲያዊ ባህሪያት መካከል አንዱ የተመዝጋቢዎችን ቁጥር (turn out) ማየት ነው፡፡ ዕድሜያቸው ለምርጫ ከደረሱ ዜጎች እስከ 70 በመቶ ወጥተው ድምፃቸውን ከሰጡ የሕዝቡ ተሳትፎ ከፍተኛ መሆኑን አመላካች ነው፡፡ ሕዝቡም ለሚሰጠው ድምፅ ከፍተኛ ዋጋ መስጠቱን የሚያመላክተው የሚሰጠው ድምፅም በትክክል ይቆጠራል፣ ለውጥም ያመጣል በሚል እምነት የታጀበ ነው፡፡

የተመዝጋቢው ቁጥር በተለይ ደግሞ ተመዝግቦ የምርጫ ካርድ ወስዶ በምርጫው ዕለት ድምፅ የሚሰጠው ቁጥር ማነስና መብዛት ሕዝቡ በሥርዓቱ ላይ ያለውን አመኔታም አመላካች ነው፡፡ ድምፄ በትክክል አይቆጠርም የሚል ግምትና እምነት ካደረበት የመራጭ ካርድም ወስዶ ድምፁን መስጠት እንደ ከንቱ ልፋት ስለሚቆጥረው ሒደቱን ከቁብ አይቆጥረውም፤ አይመዘገብም፤ ከተመዘገበም ድምፅ ላይሰጥ ይችላል፡፡ ድምፄ ይጭበረበራል በሚል፡፡ ወይም ደግሞ እንደ ወ/ሮ ዘርዬ ለምን እንደሚመርጥም መረጃ የለውም፡፡

የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ በ2005 ዓ.ም. በሚካሄደው የአካባቢ፣ የአዲስ አበባና የድሬዳዋ መስተዳደር ምክር ቤቶች ምርጫ ከታኅሳስ 22 አስከ ጥር 21 2005 ዓ.ም.፣ እንዲሁም ደግሞ ጊዜውን በማራዘም ጥር 24 እና 25 ቀን 2005 ዓ.ም. ባካሄደው የምዝገባ ወቅት ቀድሞ ያስቀመጠው ግምትና ተመዘገበ ያለውን የሕዝብ ቁጥር አነፃፅሮ አስቀምጧል፡፡ ቦርዱ ከማዕከላዊ ስታትስቲክስ ባገኘው መረጃ መሠረት፣ በአሁኑ ወቅት የኢትዮጵያ ሕዝብ ቁጥር 86 ሚሊዮን የሚገመት ሲሆን፣ ከዚህ ውስጥ ዕድሜው ለመራጭነት የደረሰው 40 በመቶ (34.5 ሚሊዮን) ነው፡፡ ከእነዚህ መካከል ተመዝግበው ካርድ ይወስዳሉ ብሎ የገመተው 83 በመቶ ወይም 28.5 ሚሊዮን ሕዝብ እንደነበር በመረጃ ሰንጠረዡ አስፍሯል፡፡

ቦርዱ ባካሄደው ምዝገባ 30.6 ሚሊዮን ሕዝብ የምርጫ ካርድ የወሰደ ሲሆን፣ ይኼም በቦርዱ ቀድም ሲል ከተገመተው 83 በመቶ አልፎ 88.93 በመቶ ደርሷል፡፡

ካለፉት ምርጫዎች ጋር  ሲነፃፀር ዘንድሮ ምርጫ ቦርድ ይፋ ያደረገው የመራጮች ቁጥር እጅግ ከፍተኛ የሚባል ነው፡፡ ዋናው ጉዳይ ምርጫ ቦርድ የመዘገበው ቁጥር እውነት ነው ወይ አይደለም በማለት በርካቶች የሚያነሱት ጥያቄ ነው፡፡ ይህንን ጥያቄ ለማንሳት ምክንያት የሚሆኑ ሁለት መሠረታዊ ነገሮችን ማንሳት ይቻላል፡፡ አንደኛው ምርጫው ሊካሄድ የቀረው ጊዜ ከአንድ ወር የማይበልጥ ቢሆንም፣ በሕዝቡ ውስጥ ‹‹ምርጫ ምርጫ›› የሚሸት መንፈስ አለመኖሩ ነው፡፡ በማኅበራዊ ሚዲያ (ፌስቡክም ሆነ ትዊተር) በርካታ ኢትዮጵያዊያን ስለ ኬንያ ምርጫ በርካታ ነገሮች ሲጽፉና ሲወያዩ እየተስተዋለ ነው፡፡ ከዚህ በፊት የተካሄደው የኬንያ ምርጫ ለበርካታ ኬንያውያን ሞት ምክንያት የነበረ ሲሆን፣ በንፅፅር የአሁኑ ሰላማዊና ብዙም ትችት ያልቀረበበት ነው፡፡ ጠቅላይ ሚኒስትር ራይላ ኦዲንጋን አሸንፈው ቀጣዩ የኬንያ ፕሬዚዳንት የሚሆኑት ኡሁሩ ኬንያታ ናቸው፡፡ ስለኢትዮጵያ መጪው ምርጫ አንስቶ የሚወያይ ግን እስከዚህም ነው፡፡

በኢትዮጵያ በቅርቡ የሚካሄደው ምርጫ የመንግሥት ለውጥ የሚደረግበትና አዲስ መሪ ለማየት የሚጓጓበት ባይሆንም፣ የዲሞክራሲያዊ ምርጫ ዋና መገለጫ የሚሆነው የሕዝብ ተሳትፎ ግን ከዋናው ምርጫም የበለጠ ክብደት ሊሰጠው በተገባ ነበር፡፡ ሕዝቡ ከክፍለ ከተማ ጀምሮ እስከ ቀበሌ ድረስ ያሉ የቅርብ አስተዳዳሪዎቹን በቀጥታ የሚመርጥበት በመሆኑ፣ የሕዝቡ ዋና ቅሬታዎች የሆኑት የፍትሕና የመልካም አስተዳደር ችግሮች የሚታዩበት የመንግሥት አስተዳደር እርከንም ነው፡፡

መንግሥት፣ ኢሕአዴግና ቦርዱ ሕዝቡ የምርጫውን አስፈላጊነት ሙሉ ግንዛቤ አግኝቶ ተመዝግቦ ከሚቀርቡለት ዕጩዎች መካከል ለመምረጥ መዘጋጀቱን እየተናገሩ ነው፡፡ አንድ ማስረጃቸውም፣ ካርድ የወሰደው የሕዝብ ቁጥር ከፍተኛ መሆኑን በመጥቀስ ነው፡፡ ተመዘገበ በሚባለው መራጭ ቁጥር ላይ ጥርጣሬ ያላቸው ሰዎች ግን ሕዝቡ ውስጥ ስለምርጫው ያለው ስሜት የሞተ መሆኑን ይናገራሉ፡፡

ከዚህም ጋር በተያያዘ ሌላ ጥርጣሬ ያላቸው አሉ፡፡ በተደጋጋሚ በገለልተኝነቱ ላይ ጥያቄ የሚነሳበት ምርጫ ቦርድ፣ መንግሥትን (ኢሕአዴግን) ለማስደሰት ቁጥሩን ከፍ አድርጎ አለመሆኑን ምንም ማረጋገጫ የለም ይላሉ፡፡ ሕዝቡ በምርጫ ሒደት ተስፋ የቆረጠ የሚመስል ሁኔታ እየተስተዋለበት ሲሆን፣ በምርጫ ወቅት የቀበሌ ሠራተኞች (ካድሬዎች) ቤት ለቤት ባደረጉት ቅስቀሳ በተፅዕኖና መንግሥትን በመፍራት ካርድ የወሰደው ይበዛል የሚል ግምት ያላቸውም አሉ፡፡ የምርጫ ቦርድ መዘገብኩት በሚለው ተመዝጋቢ ቁጥር ብዛት ተዓማኒነት ላይ ጥርጣሬ የሌላቸው ጥቂቶች ይመስላሉ፡፡

ያለ ተወዳዳሪ ምርጫ
የምርጫው ወሬ በተጀመረ ሰሞን ምርጫ ምርጫ የሚሸቱ ዜናዎችና መግለጫዎች መሰማት ጀምረው ነበር፡፡ በተለይ ምርጫ ቦርድ የምርጫው የጊዜ ሰሌዳ ላይ ለመነጋገር በሕጋዊ መንገድ ተመዝግበው የሚገኙ የፖለቲካ ፓርቲዎችን ለማነጋገር በአዳማ በጠራው ስብሰባ የተነሳ ነበር፡፡

በወቅቱ ‹‹የአገሪቱ የፖለቲካ ምኅዳር የሚያሠራ አይደለም›› በሚል ከምርጫው ፕሮግራም በፊት በእዚህ ጉዳይ ላይ ከኢሕአዴግ ጋር ቁጭ ብለው ለመነጋገር ጥያቄ ያቀረቡ ከ40 በላይ የፖለቲካ ፓርቲዎች ድምፃቸውን አሰምተው ነበር፡፡ ከእነዚህም መካከል በተለይ ‹‹33ቱ›› የሚባሉት የጋራ ጊዜያዊ ኮሚቴ በማቋቋም ቅሬታቸውን አግባብ ባለው መንገድ ለምርጫ ቦርድና ለሚመለከተው የመንግሥት አካል አቅርበው ሰሚ አለማግኘታቸውን በተደጋጋሚ ተናግረዋል፡፡

ዕጩዎች የምርጫ ምልክት የሚወስዱበት ቀነ ገደብ ቢጠናቀቅም፣ ፓርቲዎቹ ከምርጫ ውድድር ውጪ ሆነዋል፡፡ በዚህ ቡድን ውስጥ የተሰባሰቡ የፖለቲካ ፓርቲዎች መድረክንና መኢአድን ጨምሮ ዋና የሚባሉ የተቃዋሚ ስብስቦች የሚገኙበት ነው፡፡ መንግሥት 29 የፖለቲካ ፓርቲዎች የመወዳደሪያ ምልክት ወስደው ለዕጩነት መዘጋጀታቸውን ቢገልጽም፣ ከዚህ የሚበልጥ ቁጥርና ተቀባይነት ያላቸው ተቃዋሚዎች ወደ ሒደቱ ለመምጣት ምንም ጥረት አላደረጉም፡፡ የኢትዮጵያውያን ዲሞክራሲያዊ ፓርቲ (ኢዴፓ) አንድ ዕጩ በማቅረብ በአዲስ አበባ ቂርቆስ ክፍለ ከተማ ለመወዳደር የወሰነው በምርጫው ሒደት አምኖበት እንዳልሆነ በቅርቡ በሰጠው ጋዜጣዊ መግለጫ አስታውቋል፡፡ ከምርጫው ሒደቱ ራሱን ለማግለል የወሰነው፣ እንደ ፓርቲ ለሦስተኛ ጊዜ ራሱን ከምርጫ ካገለለ በሚቀጥለው ምርጫ መሳተፍ ስለማይችል ነው፡፡ በመሆኑም በዚህ የሕግ ተፅዕኖ ምክንያት በሒደቱ የሚሳተፈው ኢዴፓ፣ ከምርጫው ራሱን እንዳገለለ ነው የሚታሰበው፡፡

የተቀሩት ተቃዋሚ የፖለቲካ ፓርቲዎች አንድም በሕዝብ አይታወቁም፣ አለበለዚያም ከኢሕአዴግ አንዳንድ ጥቅማ ጥቅሞች ስለሚጠብቁ በሕዝብ ያላቸው ተቀባይነትም እስከዚህም ነው የሚሉ አሉ፡፡ በምርጫው ያላቸው ሚናም ለሕዝቡ አማራጭ ሆነው ይፎካከራሉ ሳይሆን፣ ኢሕአዴግን በሒደቱ በማጀብ ከዓለም አቀፍ ነቀፌታ መታደግ ብቻ ነው ተብለው የሚታመኑ ናቸው፡፡ በዚህም ሒሳብ አንድም የሚታወቅ ተቃዋሚ የማይወዳደርበት የአካባቢ ምርጫ፣ ያለተቃዋሚ የሚደረግ ምርጫ ነው ለማለት የሚያስደፍር ነው፡፡

የ97 ጦስ
አቶ አበራ ዘገዬ ዕድሜያቸው 56 ሲሆን የእንጨት ሥራ ባለሙያ ናቸው፡፡ ‹‹የአዲስ አበባ ምክር ቤት ምርጫ ወትሮም ቢሆን የተጋነነ ሁኔታ አይታይበትም፡፡ በእርግጥ ብሔራዊ ምርጫውም ቢሆን ከ97 ዓ.ም. በኋላ ያን ያህል አጥጋቢ አይመስለኝም፤›› በማለት ተስፋ በመቁረጥ ስሜት ይናገራሉ፡፡ ‹‹ሰሞኑን ተጀመረ የተባለውን የምረጡኝ ቅስቀሳ ግን ልብ ብዬ ሰምቼውም አላውቅም፡፡

 ይህ ደግሞ የኔ ብቻ ሳይሆን የአብዛኛው ሰው ስሜት ይመስለኛል፡፡ ምክንያቱም ማንም ሰው ስለጉዳዩ ሲያወራ አይታይም፡፡ በአጠቃላይ የምክር ቤትና የአካባቢ ምርጫ ከመሆኑ ጋር ተያይዞ ቅዝቀዝ ያለ ሁኔታ ነው ያለው፡፡ እኔ በአግባቡ በተመቸኝ ሰዓት ሄጄ ነው የምርጫ ካርዴን የወሰድኩት፡፡ የማውቃቸው ሌሎች ብዙ ሰዎች ግን ኑ ውሰዱ ተብለው እንደወሰዱ አውቃለሁ፤›› ብለዋል፡፡ በኢትዮጵያ ሞቅ ሞቅ ያለ ቅድመ ምርጫና የምርጫ ወቅት የታየበት ሦስተኛው አገራዊ የ97 ምርጫ ተጠቃሽ ነው፡፡ ሆኖም ምርጫውን ተከትሎ በተፈጠረው የፖለቲካ ቀውስ ኅብረት ፈጥረው ገዥውን ፓርቲ ተፈታትነው የነበሩ ተቃዋሚዎች ተበታትነዋል፡፡ በምርጫው ማግስት በፀደቁት አንዳንድ አፋኝ ሕጎች የተወሰዱ አስተዳደራዊ ዕርምጃዎች ተከትሎ በ2000 ዓ.ም. የተደረገው የአካባቢ ምርጫ ጀምሮ ነበር ኢሕአዴግ የፖለቲካ ሁኔታውንና የምርጫውን ሒደት ሙሉ ለሙሉ መቆጣጠር የቻለው፡፡

በወቅቱ እስከ አምስት ሚሊዮን አባላት የመለመለው ኢሕአዴግ፣ ለአካባቢ ምርጫ በአጠቃላይ እስከ ሦስት ሚሊዮን መቀመጫዎች እንዲቀርቡ ያደረገ ሲሆን፣ በወቅቱ ጠንካራ ከነበሩ ተቃዋሚዎች ኅብረትና ኦፌዲን ራሳቸውን ከሒደቱ ሲያገሉ፣ ኢዴፓ ለተሳትፎ ሲል ተወዳድሯል፡፡ በቅንነት የተደረገ ምርጫም አልነበረም በማለት የሚተቹ ብዙ ናቸው፡፡

ቀጥሎም በተካሄደው የ2002 ዋና ምርጫ መድረክ የተባለው የፖለቲካ ፓርቲዎች ስብስብ ሆኖ ብቅ ያለ ቢሆንም፣ ከአንድ የፓርላማ መቀመጫ ውጪ ማግኘት አልቻለም፡፡ ከምርጫው በፊት ጀምሮ የፖለቲካ ምኅዳሩ የማያፈናፍን ሆኗል በሚል የሚቀርብበትን ትችት ጆሮ ዳባ ልበስ ያለው ኢሕአዴግ፣ ሒደቱ በነበረበት ቀጥሎ ዋናዎቹ ተቃዋሚዎች ከምርጫ ውጪ ሆነው፣ ሕዝቡ በተፅዕኖ የምርጫ ካርድ የሚወስድበትና የደበዘዘ የምርጫ ሒደት የሚታይበት የአሁኑ ወቅት ላይ መደረሱን ተቃዋሚ የፖለቲካ ፓርቲዎችና ተቺዎች የሚስማሙበት ነው፡፡

የብዙ አስተያየት ሰጪዎች ሥጋት የፖለቲካ ምኅዳሩ አሁን ባለው ሁኔታ የሚቀጥል ከሆነ ሕዝቡም ሆነ ዋነኛ ተቃዋሚዎች በምርጫ መንግሥት መለወጥ አይቻልም የሚል ሙሉ ሙሉ ተስፋ መቁረጥ እንዳያስከትል ነው፡፡ በዚህም ምክንያት በሰላማዊ መንገድ ኢሕአዴግን መቃወምና መታገል አይቻልም የሚል ስሜት ሊፈጠር እንደሚችል ይታመናል፡፡ ኢሕአዴግ ምርጫን ሥልጣኑን ለማራዘም የሚጠቀምበት ስልት ነው በሚል ነፍጥ የሚያነሱ አማፂዎች የበለጠ ድጋፍ እያገኙ ሊሄዱ ይችላሉ የሚል ሥጋትም አለ፡፡

No comments:

Post a Comment