Feb 19, 2013

የቀድሟ ቀዳማዊ እመቤት ወ/ሮ አዜብ መስፍን በቂርቆስ ክፍለ ከተማ በምርጫ እንደምትወዳደር ሲገለጽ የቀድሞ የሥራ ኃላፊዎች እስከ 24 ዓመት በሚደርስ ፅኑ እስራት ተፈረደባቸዉ


B. Tsegaye Norway ( ፈብ 17)

የቀድሟ ቀዳማዊ እመቤት ወ/ሮ አዜብ መስፍን ከዚህ ቀደም በምርጫ ትወዳድርበት የነበረውን የትግራይ ክልል በመተው በአዲስ አበባ ከተማ ለምርጫ እንደምትቀርብ ከወደ አዲስ አበባ የመጡ ዜናዎች አመለከቱ። 
“የአቶ መለስ ዜናዊን ሌጋሲ እኔ አስፈጽመዋለሁ” በሚል በአቶ መለስ የቀብር መታሰቢያ ፕሮግራም ላይ በድፍረት የተናገረችው ወ/ሮ አዜብ በአሁኑ ወቅት የፌደራሉ ፓርላማ አባል ብትሆንም ኢሕአዴግን ወክላ በመጪው የቀበሌና የወረዳ ምርጫ ላይ ኢሕ አዴግን በመወከል በበቂርቆስ ክፍለከተማ እንደምትወዳደር የዘ-ሐበሻ የአዲስ አበባ ዘጋቢዎች አስታውቀዋል።

በተለይ “አፍቃሬ ኢሕአዴግ” በመባል የሚታወቀው የአቶ ልደቱ አያሌው ኤዲፓ በዚህ ምርጫ ላይ ሙሉ በሙሉ ሳይሆን በከፊል ብቻ እንደሚሳተፍ ባሳወቀበት በዘንድሮው ምርጫ ከወ/ሮ አዜብ ጋር ይወዳደራል ተብሎ የሚጠበቀው የኢዴፓው ወንድወሰን ተሾመ ነው። አቶ ወንደሰን ተሾመ ኢዴፓ ብቸኛው ያቀረበው እጩ ሲሆን ይህም እጩ ከወ/ሮ አዜብ በሚወዳደሩበት የምርጫ ጣቢያ እንዲወዳደር የተደረገው የፖለቲካ ትርፍ ኢሕአዴግ ለማግኘት አስቦ ነው ሲሉ አስተያየት ሰጪዎች ትዝብታቸውን ለዘ-ሐበሻ ይገልጻሉ።
ባልተለመደ መልኩ ከትግራይ ክልል ተነስታ በአዲስ አበባ ከተማ ለምርጫ የምትወዳደረው ወ/ሮ አዜብ ምርጫው የተበላ እቁብ በመሆኑ በቀጥታ አሸንፋ የአዲስ አበባ ካቢኔ ውስጥ በመግባት የኦሕዴዱን ኩማ ደመቅሳ ቦታ በመቀበል የከተማዋ ከንቲባ እርሷን ለማድረግ የታቀደ ነገር እንዳለ ያስታውቃል ያሉት ታዛቢዎች በተለይም ከሰሞኑ ከወ/ሮ አዜብ ጋር ቅርርብ አላቸው የተባሉ አንዳንድ የአዲስ አበባ መጽሔቶች “የሴት ጠ/ሚ/ር ማየት ናፈቀን” የሚል ጽሁፍ ሁሉ መጻፉን ከወ/ሮ አዜብ ወደ አዲስ አበባ ከንቲባ መምጣት ጋር አያይዘውታል – ታዛቢዎቹ።
አቶ አርከበ እቁባይ የአዲስ አበባ ከተማ ከንቲባ በነበሩበት ወቅት በአዲስ አበባ የታዩ ለውጦችን ቢያደርጉም የአዲስ አበባ ሕዝብ በምርጫ 97 ወቅት “አርከበ ለከተማዋ እድገት ብትጥርም፤ ኢሕአዴግን ወክለህ ብቻ ስለመጣህ አንመርጥህም” የሚል ምላሽ ከህዝቡ አግኝቶ ኢሕአዴግ በምርጫው በ0 በተሸነፈበት ወቅት ከወ/ሮ አዜብ ጋር እንደማይዋደዱ የሚነገርላቸው አቶ አርከበ በባልየው በአቶ መለስ ዜናዊ “በአዲስ አበባ ላይ ቀለም ከመቀባት በስተቀር ያመጣኸው ለውጥ የለም” በሚል በስብሰባ ላይ በግልጽ ተሰድበው ነበር።
በአሁኑ ወቅት ሕወሃት በክፍፍል ላይ እንዳለ እየተዘገበ መሆኑ ይታወቃል። የአቶ ስብሃት እና የወ/ሮ አዜብ ግሩፕ በየፊናው ተፋጧል። አሁን ወ/ሮ አዜብን በአዲስ አበባ ከንቲባነት አማሎ ድርጅቱን የማዳን ሥራ እየተሰራ ነው የሚሉ የፖለቲካ ተንታኞች አሉ። ይህ በዚህ እንዳለ 
የፌዴራል የሥነ ምግባርና የፀረ ሙስና ኮሚሽን ክስ የመሠረተባቸው የቂርቆስ ክፍለ ከተማ የቀድሞ የሥራ ኃላፊዎች በመንግሥት ላይ ከአራት ሚሊዮን ብር በላይ ጉዳት አድርሰዋል በማለት እስከ 24 ዓመት በሚደርስ ፅኑ እስራትና በገንዘብ እንዲቀጡ የፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት የካቲት 6 ቀን 2005 ዓ.ም. በዋለው አንደኛ ወንጀል ችሎት ውሳኔ አስተላለፈ፡፡


የኮሚሽኑ ዓቃቤ ሕግ ክስ መዝገብ እንደሚያስረዳው፣ 1ኛ ተከሳሽ ማዘንጊያ ካሳ በቂርቆስ ክፍለ ከተማ የፋይናንስና ኢኮኖሚ ጽሕፈት ቤት ኃላፊ፣ 2ኛ ተከሳሽ ሲሳይ አያሌው ዋና ሥራ አስፈጻሚ፣ 3ኛ ተከሳሽ ገብረ እግዚአብሔር ገብረ ማርያም ምክትል ዋና ሥራ አስፈጻሚ፣ 4ኛ ተከሳሽ ደስታ ሎሬንሶ የንግድና ኢንዱስትሪ ጽሕፈት ቤት ኃላፊ፣ 5ኛ ተከሳሽ ተስፋዬ ነጋሽ የትምህርት ጽሕፈት ቤት ኃላፊ፣ 9ኛ ተከሳሽ ጌታሰው ጋሻው የሥራና የከተማ ልማት ጽሕፈት ቤት ኃላፊ፣ 10ኛ ተከሳሽ ራሔል ሙሉጌታ የሴቶች ጉዳይ ጽሕፈት ቤት ኃላፊ፣ 11ኛ ተከሳሽ ሊዲያ ሳንቴ የባህልና ቱሪዝም ጽሕፈት ቤት ኃላፊ፣ 12ኛ ተከሳሽ ንጉሴ ፈንቴ የንብረት አስተዳደርና ጠቅላላ አገልግሎት ክፍል ኃላፊ የነበሩ ተከሳሾች፣ ዘለዓለም ክንፈ ከተባለ 15ኛ ተከሳሽ ጋር በመተባበር በሥልጣን ያለአግባብ መገልገል የሙስና ወንጀል ፈጽመዋል፡፡ 

በተከሳሾቹ ላይ በአንድ የክስ መዝገብ አሥር ክሶች የተመሠረቱ ሲሆን፣ በ1ኛ ክስ 2ኛ፣ 3ኛ፣ 4ኛ፣ 5ኛ፣ 9ኛ፣ 10ኛ እና 11ኛ ተከሳሾች የመንግሥት ግዥ ከ250 ሺሕ ብር በላይ በግልጽ ጨረታ መከናወን እንዳለበት እያወቁ በተቃራኒው የመንግሥትን የግዥ አዋጅ፣ መመርያና አሠራር በመተላለፍ ግዥው በንግድና ኢንዱስትሪ ተመዝግቦ ከማይታወቅ ከአንድ ሕገወጥ ድርጅት እንዲፈጸም መወሰናቸውን ክሱ ያስረዳል፡፡ በ2ኛ ክስ 1ኛ፣ 12ኛ እና 15ኛ ተከሳሾች የመንግሥት ግዥ በቁጠባና ውጤታማ መንገድ እንዲፈጸም ከማድረግ ይልቅ ከሕገወጥ ግለሰቦችና ድርጅቶች ጋር ሕገወጥ የጥቅም ግንኙነትን በመፍጠርና ትዕዛዞችን በመስጠት መንግሥት ያለአግባብ ወጪ እንዲያወጣ አድርገዋል፡፡ 

በ4ኛ እና በ8ኛ ክሶች 15ኛ ተከሳሽ የሕዝብና የመንግሥትን ጥቅም ለመጉዳት ከክፍለ ከተማው የሥራ ኃላፊዎች ጋር ተመሳጥሮ በንግድና ኢንዱስትሪ ጽሕፈት ቤት የማይታወቁ ድርጅቶችን በመፍጠር እንዲሁም ሐሰተኛ ሰነዶችን በማዘጋጀትና በመገልገል በሕገወጥ ግዥ የተገኘው ገንዘብ ወደ ሕገወጥ ድርጅቶች እንዲገባ አድርጓል፡፡ በ5ኛ እና በ5ኛ ክሶች 1ኛ እና 2ኛ ተከሳሾች ደግሞ በደመወዛቸው ከሚያገኙት ገንዘብ በላይ አካብቶ በመገኘታቸው በፈጸሙት ምንጩ ያልታወቀ ገንዘብ አካብቶ መገኘት የሙስና ወንጀል ተከሰዋል፡፡ በ9ኛ እና በ10ኛ ክሶችም እነዚሁ ተከሳሾች የሥራ ኃላፊነታቸውን ወደ ጎን በመተው ከሌሎች ግብረ አበሮቻቸው ጋር በመሆን ሕገወጥ ግለሰብና ድርጅቶችን ለመጥቀም በማሰብ በመንግሥት ላይ ከፍተኛ ጉዳት እንዳደረሱ ታውቋል፡፡ 

በአጠቃላይ ተከሳሾቹ በ2001 ዓ.ም. በተለያዩ ጊዜያት ባካሄዱዋቸው ስብሰባዎች ባሳለፏቸው የግዥ ውሳኔዎች በድምሩ ከ18.4 ሚሊዮን ብር በላይ ወጪ ሆኖ የተለያዩ የቢሮ መገልገያ ዕቃዎችና የዕድሳት ግዥዎችን ከአሠራርና ከመመርያ ውጪ እንዲፈጸሙ አድርገዋል፡፡ በዚህም ምክንያት ጥራታቸውን ያልጠበቁ ዕቃዎችን በተጋነነ ዋጋ እንዲቀርቡ በማድረግ በመንግሥት ላይ ከ4.4 ሚሊዮን ብር በላይ ጉዳት በማድረስ ሕገወጥ ግለሰቦችና ድርጅቶች እንዲጠቀሙ ማድረጋቸውን የክስ መዝገቡ ያስረዳል፡፡ 

በመሆኑም 1ኛ ተከሳሽ ማዘንጊያ ካሳ በሦስት ክሶች በድምሩ በ24 ዓመት ከሦስት ወራት ፅኑ እሥራትና 20 ሺሕ ብር፣ 2ኛ ተከሳሽ ሲሳይ አያሌው በሦስት ዓመት ፅኑ እስራትና 2,500 ብር፣ 3ኛ፣ 4ኛ፣ 5ኛ፣ 9ኛ፣ 10ኛ እና 11ኛ ተከሳሾች እያንዳንዳቸው በአንድ ዓመት እስራት፣ 12ኛ ተከሳሽ ንጉሴ ፈንቴ በስድስት ዓመት ፅኑ እስራትና አራት ሺሕ ብር፣ 15ኛ ተከሳሽ ዘለዓለም ክንፈ በ18 ዓመት ከአምስት ወራት ፅኑ እስራትና 20 ሺሕ ብር እንዲቀጡ ፍርድ ቤቱ የካቲት 6 ቀን 2005 ዓ.ም. በዋለው 1ኛ ወንጀል ችሎት ውሳኔውን ያስተላለፈ ሲሆን፣ ከወንጀሉ ጋር ተያይዞ ለመንግሥት የሚመለስ የገንዘብና ንብረት ጉዳይም በፍርድ ቤት ተይዞ በሒደት ላይ የሚገኝ መሆኑ ታውቋል፡፡ 

No comments:

Post a Comment